2015 ሜይ 6, ረቡዕ

ሰበር ዜና – ቅዱስ ሲኖዶስ በሊቢያ ለተሠዉት ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች የሰማዕትነት ሥያሜ ሰጠ


ethiopian Orthodox martyrs
  • ዝርዝር መግለጫው በይፋ የሚወጣው በቀጣዩ የጥቅምት ምልዓተ ጉባኤ ነው
  • በስደት ያሉ የሚመለሱበትና በኑሯቸው የሚቋቋሙበት ጠንካራ ውሳኔ ተወስኗል
  • ከልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ጋራ የሚሠራ ኮሚቴ ይቋቋማል
በሊቢያ፣ ‹‹ሃይማኖታችን አንክድም፤ ማዕተባችንን አንበጥስም›› ብለው በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነታቸው በመጽናታቸው፣ ራሱንእስላማዊ መንግሥት(ISIS) ብሎ በሚጠራው ዓለም አቀፍ አሸባሪ ቡድን በሰይፍ ተቀልተው እና በጥይት ተደብድበው የተገደሉት ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች የሰማዕትነት ሥያሜ እንዲሰጣቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወሰነ፡፡
የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በአረመኔያዊ አኳኋን የተገደሉት ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን ሰማዕት እንዲባሉ የወሰነው፣ በዛሬው ሚያዝያ ፳፰ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. የመጀመሪያ ቀን የቀትር በኋላ ውሎው በጉዳዩ ላይ በስፋት ከመከረበት በኋላ ነው፡፡
በሊቢያ የሜዲትራንያን ባሕር ዳርቻ እና በረሓ በወሩ መጀመሪያ ስለ እምነታቸው መሠዋታቸው የታወቁት ኦርቶዶክሳውያን፣ ‹‹ወኩን መሃይምነ እስከ ለሞት ወእሁበከ አክሊለ ሕይወት = እስከ ሞት ድረስ የታመንኽ ኹን የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለኹ›› /ራእይ ፪፥፲/ ያለውን የጌታችን ቃል ጠብቀው ሃይማኖታችንን አንክድም በማለት የሃይማኖት ሰማዕትነትን የተቀበሉ የሃይማኖት መስተጋድላን እንደኾኑ የግድያው ዜና በተሰማበት ማግሥት በቋሚ ሲኖዶስ መገለጹ ይታወሳል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ በሚያዝያ ፲፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. መግለጫው በአይ.ኤስ አሸባሪ ቡድን በግፍ የተገደሉት ልጆቻችን ቤተ ሰዎች ኹሉ የሰማዕታቱን ስመ ክርስትና፣ ሥዕለ ገጽ(ፎቶ) እና ሙሉ አድራሻ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት በተቻለ ፍጥነት እንዲያቀርቡ አሳስቦ ነበር፡፡
በሃይማኖታቸው ምክንያት ለተሠዉት ክርስቲያኖች ሊሰጥ የሚገባው የሰማዕትነት ክብር(ማዕርግ) መኾኑን በውሳኔው ያመለከተው ምልዓተ ጉባኤው፣ ስለ ሥያሜው እንዲኹም እያንዳንዳቸው ስለተሠየሙበት የሰማዕትነት ማዕርግ እና ክብር ዝርዝር መግለጫ የሚሰጠው በመጪው ዓመት ጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንደሚኾን በውሳኔው ማመልከቱ ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል ምልዓተ ጉባኤው በዛሬው ውሎው፣ በስደት ያሉ ኢትዮጵያውያን ወገኖች እና የቤተ ክርስቲያን ልጆች ሊቢያን ጨምሮ ለጥቃት ከተጋለጡባቸው አካባቢዎች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ቤተ ክርስቲያን ጠንካራ ግፊት ከማሳደር ጀምሮ ተመላሾችን በማቋቋም ረገድፋይናንሳዊ፣ ማኅበራዊ እና ሥነ ልቡናዊ ድጋፎችን ማድረግ እንደሚኖርባት የሚገልጽ ጠንካራ ውሳኔ ማሳለፉ ታውቋል፡፡
ውሳኔውን የሚያስፈጽም ራሱን የቻለ አካል የሚቋቋም ሲኾን፣ ይኸው አካል ተግባሩን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ጋራ በመተባበር እንደሚፈጽም ተጠቅሷል፡፡ የስደተኞች እና ተመላሾች ጉዳይን በመምሪያ ደረጃ አቋቁሞ በቀጥተኛ እና በተዘዋዋሪ መንገድ ተጠቃሚ ለማድረግ የሚሠራው ኮሚሽኑ፣ ቀደም ሲል የገንዘብ አስተዋፅኦ የሚሰበሰብበት አካውንት በመክፈት ገባሬ ሠናይ አካላትን ማነጋገር መጀመሩ ተገልጧል፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...